...

The African Building Platform

Trending

ስለ ከተማ – ጥያቄ

መነፅር ፤
Medhanit Ayele
Share on facebook
Share on twitter
Share on linkedin
Share on telegram

ያ’ዲስ አበባ ሴቶች የት እየሸኑ ነው?

ያዲስ አበባ ሴቶች የት እየሸኑ ነው?
መቼስ የተፈጥሮ ህግ ነውና በቀን ውሏችን ቢያንስ አንዴ የመፀዳጃ ቤት ሳንጎበኝ አንውልም። እንዲህ ከሆነ ታዲያ ለሴቶችም ሆነ ለወንዶች በቂ የመፀዳጃ ስፍራ በከተማችን አዲስ አበባ ማስፈለጉ አያጠራጥርም። ነገር ግን በቂ የመፀዳጃ ስፍራ የሌላት ከተማችን በብዛት የወንዶችን ሽንት በየመንገዱ ስታስተናግድ፣ ሴቶች የት እየሸኑ እንደሆነ ግር ቢላት አይደንቅም።

ታዲያ “የአዲሳ’ባ ሴቶች ሆይ የት እየሸናችሁ ነው፤ እስኪ ወንዶቹንም ምሩልን”።

ነገር ግን ይህን ጠይቀን ሳናበቃ በከተማዋ በብዙ ህንፃዎች ውስጥ የተዘጉት የሴቶች መፀዳጃ ክፍሎች ይወቅሱናል። ሴቶች ታዲያ በቂ የመፀዳጃ ስፍራ ኖሯቸው ሳይሆን እንዲያው የተፈጥሮ ነገር ቢከለክላቸው ከከተማዋ ሁኔታ ጋር እራሳቸውን አጣጥመው ስለኖሩ እንጂ ስለተመቻቸው እንዳልሆነ ግልፅ ነው። ስለዚህም ለወንዶች መንገድ ላይ መሽናት መስፋፋት በቂ የመፀዳጃ ስፍራ ማነስ ሳይሆን በማህበረሰባችን ውስጥ ሰርጎ የገባው ቸልተኝነት በዋናነት ተጠያቂ ሳይሆን አይቀርም።
ታዲያ የወንዶችን በየመንገዱ ላይ መሽናት እንዴት ተቀበልነው? እንዴት የሚሸናው ሰው ሳያፍር መንገደኛው እያፈረ ዘወር ይል ጀመረ?

አንድ አዲስ አበባ የመጡ ባለ’ሀገር ከተማውን ሲዞሩ ውለው፣ ግብዣቸውን አጣጥመው ካመሹ በኋላ መፀዳጃ ቤት ይፈልጋሉ። ፈልገው ቢያጡ “አዲስ አበባማ ካበላ ያሳራ ፀደቀ!” አሉ ይባላል።

አንድ ሰካራም በአንድ ምሽት አቡነ ጴጥሮስ ሃውልት ላይ ‘አንት ድንጋይ’ እያለ ሲሸና ከእውቁ ገጣሚ ፀጋዬ ገብረ መድህን ጋር ይገጣጠማል። ድርጊቱም ‘ጴጥሮስ ያችን ሰዓት’ የተሰኘ ግጥሙን ሎሬቱ እንዲተይብ መንስኤ ሆነው።

ሰካራሙ ሽንቱን ሳይሸናበት ሀውልቱን እየተሳደበ ቢሆን ኖሮ ገጣሚው ቁጭቱ ይህን ያህል ይቀሰቀስ ነበር? ወይስ በዝምታ ሽንቱን ቢሸና ገጣሚው ያልፈው ነበር? ሀውልቱ ላይ ሽንት መሽናት ያን ያህል ብስጭት ከቀሰቀሰ በቀን በቀን በምንመላለስበት መንገዶቻችን ላይ መሽናት እንዴት ሳያበሳጨን ቀረ? ጊዜ ተቀይሮ፣ የኑሮ አዚሟ ከብዶ ማስተዋል አቅቶን ነውን? ቸል አልን፣ በቸልታችንም ተመርኩዞ ሰካራሙም ሽንቱ የወጠረውም ጎረምሳ የከተማዋን ጎዳናዎች በሽንት ያረጥቧታል።
“አጥር ላይ የሸና ይሸነሸናል መንገድ ላይ መሽናት ያስቀጣል”

ወንዶች ሽንታቸው ምን ይህል ሲያስቸግራቸው መንገድ ላይ ለመሽናት እንደሚመርጡ መለካት ቢቻል እንዴት መልካም ነበር።

ብዙሃኑ መንገድ ላይ ሽንታቸውን የሚሸኑ ወንዶች ሽንታቸውን መቆጣጠር ሲከብዳቸው ይሆን መንገድ ላይ ለመሽናት የሚገደዱት? ወይንስ መንገድ ላይ መሽናትን እንደ አንድ ሁነኛ አማራጭ መቁጠራቸው ነው ያን ያህል ሽንታቸው ሳያስቸግራቸው ለድርጊቱ የሚገፋፉት?

‘መሽናት ያስቀጣል’ ብሎ ከመፃፍ ይልቅ የተለያዩ ድርጊቱን የሚኮንኑ ምስሎችንአጥር ላይ ማድረግ ‘መንገድ ላይ መሽናትን‘ ይከላከል ይሆን?

መሽናትን ከሚከለክሉ ጥቅሶች ይልቅ ሃሳብ የሚጭሩ ምስሎች ለከተማችን መልስይዘው ይመጡ ይሆን? የምስል ጥበብ ጉልበቱ በዚህ የከተማ ላይ ተሞክሮ የሚፈተሽ ይሆናል። በጥበብ በአደባባይ የጎዳና ጥበብ ዝግጅት ላይ በመሳተፍ አዲስ የጎዳና ላይ ጥበብ ቡድን በአራት የተመረጡ የከተማችን ጎዳናዎች ላይ መሽናትን የሚከለክሉ ጥቅሶችን በማደስ በምስል በመደገፍ ሰዎች ከእነዚህ ምስሎች ጋር ካላቸው ስሜታዊ ትስስር የተነሳ ከድርጊታቸው ይቆጠቡ ይሆን በማለት የጎዳና ጥበብን በአዲስ መልኩ ይፈትሻል። መልሱ ግን እርሶ አንባቢው ምስሎቹ ባሉበት ጎዳናዎች ላይ የሚመለከቱት እውነታ ይሆናል።

በአንድ ምሽት አጋጣሚ ሆኖ ስልክ ለማናገር ከክፍሌ መስኮት ወጣ ብዬ እያለሁ ሁለት ጎረምሶች የሰፈር መንገድ ላይ መኪናቸውን አቁመው ወርደው ይንጎራደዳሉ። አቅራቢያው ወዳለው መጠጥ ቤት ያመራሉ ብዬ ስጠብቅ አንደኛው አላየኝም ነበርና አጥራችን ላይ ወዳሉ አትክልቶች ማጎብደድ ጀመረ። ወዲያውኑ ነገሩ ስላልገባኝ በዝምታ ስመለከት ቆይቼ ሊሸና እንደሆነ ስረዳ ግን ስልኬን ማቋረጥ ግድ ሆነብኝ።

“ኸረ ወንድም መኖሪያ ቤት ነው፤ ተመለስ!” ስለው መለስ ብሎ ብዙም ሳይርቅ ተሰርቶ ወዳላለቀ የጎረቤት ቤት አጥር አመራ። እራቅም አይል እያልኩ ሳስብ ጓደኛው ከጅምሩ ትንሽ ራቅ ብሎ እየሸና “እዚም አይቻልም እንዳትይ ብቻ፤ እ..እ” ይላል።

“እሱ ይሄን ያህል ደፍሮ ከቤቴ ፊት ለፊት ሲሸና እኔ እንዴት የመከልከል ጉልበት ያንሰኛል?” ብዬ እያሰብኩ በአግራሞት ብቻ ወደ ቤቴ ውስጥ ተመለስኩ።

አንድ ቀን በቅርቡ ማለትም ህዳር 2013 ውስጥ መሆኑ ነው ግዮን መናፈሻ ከስራ ሰዓቴ በኋላ ትንሽ አረፍ ለማለት ገብቼ እንዲያው ስዘዋወር የአንድ ጥበቃ ድርጊት ቀልቤን ሳበው። መኪኖች ከሚያቆሙበት አስፋልት ወደ ጀርባ ሄዶ ሽንቱን ሲሸና ተመለከትኩት። ከአንድ መልካም ጉደኛዬ ጋር ነበርኩና ሁኔታው ሳቄን አመጣው። ለምን ሳኩ?

እንዴት ‘ሳር አይርገጡ’ እየተባለ በተለጠፈበት የመናፈሻ ቦታ ጥበቃው ደቂቃዎችን ተራምዶ ሽንቱን መፀዳጃ ቤት መሽናት ያቅተዋል?

እንዴት?

Interesing article?

Check out the full journal for other interesting contents and more.

Thank you for reading Ketema, the African building platform.

Subscribe below to receive an email when a new issue is released.

Your email address will not be shared with anyone else, and it’s easy to opt out if you change your mind.

© October, 2024 Ketema Journal

Thank you for reading Ketema, the urban building platform.

Subscribe below to receive an email when a new bimonthly issue is published.

Your email address will not be shared with anyone else, and it’s easy to opt out if you change your mind.

Seraphinite AcceleratorOptimized by Seraphinite Accelerator
Turns on site high speed to be attractive for people and search engines.