...

The African Building Platform

Updates

የካቲት 12 እና የግራዚያኒ አዲስ አበባ

ህላዊ ሰውነት በሻህ (አርኪቴክት)
Helawi Sewnet Beshah (Architect)
Share on facebook
Share on twitter
Share on linkedin
Share on telegram

ጣሊያን ኢትዮጵያ ላይ ለሁለተኛ ጊዜ ወረራ አድርጎ ለአምስት አመት በተቆጣጠረበት ወቅት 1929 ዓ.ም. በየካቲት 12 እለተ አርብ ነበር። የአጼ ሀይለስላሴን ወደ እንግሊዝ መሰደድ ተከትሎ እና የሙሶሊኒን የቅኝ ግዛት ህልም እንዲያሳካ የኢትዮጵያ አስተዳዳሪ ሆኖ የተሾመው ግራዚያኒ፣ የኔፕልሱን ልዑል መወለድ አስመልክቶ ለችግርተኛ ቤተሰቦች ገንዘብ እሰጣለሁ ብሎ በገነተ ልዑል ቤተመንግስት (የዛሬው አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ስድስት ኪሎ ግቢ) በርካታ እንግዶች በተገኙበት በአዲስ አበባ ከተማ በድህነት ውስጥ የሚገኙ ነዋሪዎች እንዲሰበሰቡ አዘዘ። ከተጋባዥ እንግዶቹም መካከል የጣልያን ሹማምንት የሜትሮፖሊታን ጳጳስ አቡነ ኪርል እና ሌሎች የኢትዮጵያ መኳንንቶች ተገኝተው ነበር።

ብራማ በነበረችው በዛች የወረሃ የካቲት አርብ የተገኙትም ኢትዮጵያውያን ከጠዋት ጀምረው አንድ በአንድ ቤተመንግስቱ ግቢ መሰብሰብ ጀመሩ። እስከረፋዱም ቁጥራቸው ቀላል የማይባል ሶስት ሺህ ያህል ነዋሪዎች በተገኙበት የግራዚያኒ መረሃ ግብር ተጀመረ። የዕለቱ አጀማመር ሲታይ ሊመጣ ያለውን የሀዘን ድባብ የገመተ ሰው ይኖራል ብሎ ለማሰብ ያዳግታል። ጥቂት ቆይቶ እኩለ ቀን ገደማ ሊሆን አካባቢ በዋናው በር በኩል ቦንብ ፈነዳ፣ ሁለተኛም ፈነዳ። ገነተ ልዑል ቤተመንግስት ከየአቅጣጫው ጩኸት አስተጋባ። ሶስተኛ ቦብም ግራዚያኒ እና መኳንንቱ ከተቀመጡበት ጠረጴዛ አጠገብ ሲወረወር ግራዚያኒ ጠረጴዛ ስር ወደቀ። የተወሰኑ የጣልያኖቹን ሹማምንት መታ።

ቦምቡን የጣለው ከጣልያኖቹ ዘንድ በአስተርጉዋሚነት ይሰራ የነበረ አብርሃ ደቦጭ እና ጓደኛው ሞገስ አስገዶም የሚባሉ የኤርትራ ክፍለሀገር ተወላጅ ወጣቶች ነበሩ። በጥቅሉ ሰባት ቦምቦች ፈነዱ። ወዲያው ካርቴሲ ወደኢትዮጵያውያኑ መኩዋንንት ሽጉጡን አነጣጥሮ የመጀመሪያዋን አንድ ጥይት ተኮሰ። ካራ ቢኔሬዎችም (የጣሊያን የሲቪል ጠባቂዎች) ምሳሌውን ተከተሉ። በጥቂት ጊዜ ውስጥም ሶስት መቶ ሬሳዎች በዛ ግቢ ውስጥ ተከመሩ። ሀይለኛና ተገቢ ያልሆነ ጭፍጨፋ ነበር። ሽማግሌዎች፣ አይነስውራን፣ እግር የሌላቸው ለማኞች፣ ድሆች እናቶች እስከልጆቻቸው ነበሩበት። ሰላሳ ያህል ሰዎች ቆሰሉ። ለሶስት ሰአታት ያህል ያለቋረጥ በግቢው ውስጥ ተኩስ ተከፈተ። ከጥቂት ጊዜ በሁዋላ ባለጥቁር ሸሚዞች፣ የጣልያን ሾፌሮች የቅኝ ግዛቱ ወታደሮች በአዲስ አበባ ከተማ እየዞሩ ህዝቡን ይፈጁት ጀመር።

እዚህ ቀን ላይ እንዴት ተደረሰ የሚለውን ታሪካዊ ዳራ ወደኋላ መለስ ብለን እንመልከት። አውሮፓውያን በ1877 ዓ.ም. በጀርመን በርሊኑ ኮንፈረንስ ተገናኝተው አፍሪካን አንደቅርጫ ከተከፋፈሏት ከ11 ዓመታት በኋላ ጣልያን ኢትዮጵያን ቅኝ ለመግዛት ስትመጣ አድዋ ላይ በከፍተኛ ሁኔታ ድል ትደረጋለች። አንድ ትውልድ አልፎ ከአርባ አመታት ቆይታ በኋላ በስልጣን ላይ የነበረው የጣልያኑ ፋሽስት ሙሶሎኒ የአድዋን ቁጭት ባለመርሳቱ ከበቀል ጋር ዘመናዊ የሆነ የአየርና የምድር ጦሩን ይዞ ኢትዮጵያ በድጋሚ መጣ። በዚህ ወቅት የጣሊያን ጦር ለኢትዮጵያ ሰራዊት ብርቱ ስለሆነበት አጼ ሃይለስላሴ በሚያዝያ (May 2, 1936) ጠዋት ከአገር ይሰደዳሉ። የጣሊያኑ ሙሶሊኒም ኢትዮጵያን በስተመጨረሻ በእጁ እንዳስገባ በሮማ ለተሰበሰበው ህዝቡ በደስታ አዋጁን አሰማ።

የኢትዮጵያን ጦር ማይጨው ላይ መሸነፍ እና እንዲሁም የንጉሱን ከአገር መውጣት ተከትሎ የጣሊያኑ አስተዳደር አዲስ አበባ እስኪገባ ድረስ በመሀል በተፈጠረው ክፍተት መዲናዋ ክፉኛ በተደራጁ ሌቦች ተዘረፈች፣ ጣሊያኖቹ እንዳይጠቀሙ በሚል ብዙ ህንጻዎችም በግለሰቦች ተቃጠሉ፣ ፈረሱ። ሙሶሊኒ ከጣሊያን በሰጠው ቀጥተኛ ትእዛዝ በተጠርጣሪዎቹ ላይ የቅጣት እርምጃ አስወሰደ። ጉዳት የደረሰባት አዲስ አበባም ለወራሪዎቹ መልካም አቀባበል ያደረገች ምቹ ከተማ አልሆነችላቸውም። የጣሊያኑ ኮማንደር ባዶግሊዮ ወዲያውኑ ለሮም በላከው ቴሌግራም ላይ ሙሶሊኒ ወደኢትዮጵያ በስድስት ወራት ውስጥ ሊልካቸው ያሉትን የጣሊያናዊ ቤተሰቦች ዕቅድ ትንሽ እንዲቆጥበው መልዕክቱን አደረሰ። አዲስ አበባም የአዲሱ የፋሺስት ግዛት መዲና የመሆኗ የወደፊት ዕጣ ፈንታ አነጋጋሪ ሆነ።

የጣሊያንን መንግስት ከሚያማክሩት ባለሙያዎች ውስጥ አብዛኞቹ አዲስ አበባን መዲና አድርጎ ማስቀጠል ስህተት እንደሚሆን አስጠነቀቁ። በሸለቆዎች የተሰነጣጠቀው ተራራና ኮረብታማ የመልከአ ምድሯ አቀማመጥና ከፍታማነት አድካሚ እና ለጉልበት ስራ አዳጋች እንደሚሆንባቸው እንዲሁም ዘርዘር ያለው የከተማዋ አሰፋፈር ለትራንስፖርት ፈተና እንደሚሆን ቅሬታዎች ቀረቡ። የአፈሩ ባህሪ ተንሸራታችነት ለመሰረት ግንባታ የሚኖረው ተግዳሮት እንዲሁም የነበረው በርካታ የባህር ዛፍ ደን ለኢትዮጵያ ሽፍቶችና ታጋዮች ምሽግ እንደሚሆን ጣሊያኖቹ ሰጉ። ከሁሉም በላይ ግን በአዲስ አበባ የነበረው ብዝሃ ጥቁር አፍሪካዊና ኢትዮጵያዊ ህዝብን አፈናቅሎ ወደሌላ ቦታ ለማስፈርና የቅኝ ገዢዎቹን የመከፋፈል ፖሊሲ ለማራመድ ፈተና እንደሚሆንና እንደፋሺስቱ አመለካከት ከአገሬው ተወላጅ አሻራ የጸዳ አዲስ ከተማ መቆርቆር እንደሚያስፈልግ አመላከቱ። ለአዲስ መዲናነት ደሴ፣ ሞጆ፣ ነቀምት እና ሐረር እንደ አማራጭነት ቀረቡ። ነገር ግን በሙሶሊኒ እይታ ከአዲስ አበባ ውጪ የሆነ የዋና ከተማ ሀይሉን እና ክብሩን ለማሳየት በፍጹም አማራጭ እንደማይሆን ከለንደኑ ዴይሊ ቴሌግራፍ ጋር ባደረገው ቃለ መጠይቅ ይፋ ቢያደርግም ብዙ የቅኝ ግዛት ሹማምንቶቹ ሀሳቡን ይቀይራል የሚል ተስፋ ነበራቸው።

በመጀመሪያዎቹ ወራት የፋሽስቱ አስተዳደር የህዝብ የመንገድ ዳር ምልክቶች በጣልያንኛ ተተርጉመው እንዲጻፉ ተደረገ። የዋና ጎዳናዎች ስሞችም በሙሶሊኒ መንግስት ውስጥ በነበሩ አንዳንድ አመራሮች ስም ተሰየሙ። በየቦታውም ሆነ በየቤቱ የሙሶሊኒ ምስል እና በአንዳንድ ቦታዎች ለህዝቡ ፕሮፖጋንዳ የሚያስተላልፉ የድምጽ ማጉያዎች ተሰቀሉ። ከዚህ ጋር ተያይዞ ፋሺስቶቹ ከኢትዮጵያ ነጻነት ጋር የተያያዙ ምስሎች እና ሀውልቶችን ማስወገድ ላይ ተጠመዱ። ከነዚህም ውስጥ አራዳ ጊዮርጊስ አደባባይ ላይ የሚገኘው የምንሊክ ፈረስ ጋላቢ ሀውልት፣ ታላቁ ቤተመንግስት አጠገብ ያለው የባእታ ቤተክርስቲያን ውስጥ የሚገኘው የምኒሊክ መቃብር፣ ለገሀር ባቡር ጣቢያ ፊት ለፊት የቆመው የይሁዳ አንበሳ ሀውልት፣ በወቅቱ አዲስ አበባ ላይ የነበረ የአክሱም ሀውልት አምሳያ፣ የስላሴ ኮኮብ ሀውልት፣ እና በርካታ በወቅቱና ቀደምት የነበሩ መሪዎች ምስሎችን ያካትታል። ሙሶሊኒም በቴሌግራፍ በላከው መልዕክት “የምኒሊክ ሀውልትን መፈንዳት ይኖርበታል” ሲል አቅጣጫውን አስቀመጠ።

በወቅቱ የአገሪቱ ተጠባባቂ ገዢ ሆኖ ወደአዲስ አበባ የመጣውና በቅጽል ስሙ “የሊቢያ ጅብ” በመባል ይታወቅ የነበረው የቀድሞ ወታደሩ ግራዚያኒ ከሀውልቶቹ ጋር ተያይዞ የተሰጠውን ትዕዛዝ ለመፈጸም በማቅማማት ለጣልያኑ የቅኝ ግዛቶች ሚንስትር እንዲህ የሚል ቴሌግራፍ መልዕክት ላከ። “አዲስ አበባ እንደመጣሁ የምኒሊክ እና የይሁዳ አንበሳ ሐውልት አልተነሱም ነበር፤ ማንም የክቡርነትዎን ትዕዛዝም አላስተላለፈልኝም ነበር። ነገር ግን አሁን እንዲህ አይነቱ እርምጃ ማስተዋል ያለበት አይመስለኝም፣ በተለይ ተከትሎኝ ከመጣው መጥፎ ስሜ አንጻር። እናም ስኬታማ የሆነ ፖለቲካዊ ውጤት የማመጣ ከሆነ የበረደ አካሄድ መከተል ይኖርብኛል፤ በተለይ የዚህ አይነቱ እርምጃ ከሚነጥለን ከቤተክህነት ጋር፣” በማለት ስጋቱን ገለጸ።

በእንደዚህ አይነት ምክንያት ያልተደነቀው ሙሶሊኒ፣ ውሳኔው በአፋጣኝ እንዲፈጸምለት በድጋሚ ስላዘዘ በሀያ አራት ሰዐት ውስጥ የምኒሊክን እና የይሁዳ አንበሳን ሐውልት እንድታነሳ የሚል ትዕዛዝ ለግራዚያኒ በቴሌግራፍ ደረሰው። ከእንደዚህ አይነት ዱብ እዳ ጋር የተጋፈጠው ግራዚያኒ ትዕዛዙን እንደሚፈጽም ነገር ግን ጊዜ እንደሚያስፈልገው ጠቅሶ ለቅኝ ግዛት ሚንስትር ድኤታው ጻፈ። “እለምንዎታለሁ ክቡርነትዎ፤ የሚንስትሩን ትዕዛዝ እንደምፈጽም ያረጋግጡልኝ። ነገር ግን ሁለቱም ሀውልቶች በርካታ ቶን የሚመዝኑ እንደመሆናቸው፣ ከቆሙበት የማንሳቱ ስራ ባለሙያዎችን እና በርካታ ቀናት ይፈልጋል፣” ሲል በድጋሚ ተማጸነ። ከበርካታ ወራት በኋላ ስራው በጥቅምት 6 ሌሊት ላይ ተጠናቀቀ።

ኢትዮጵያውያኑ ከእንቅልፋቸው ተነስተው የምኒሊክን ሀውልት መነሳት ሲያዩ እጅግ ተቆጡ። በአደባባይ ላይ በርካቶች በእንባ ተራጩ። “ምኒሊክን አበቃ። በሌሊት ሰረቁት” ሲሉ አለቀሱ። ህዝቡ ሲሰበሰብ የጣሊያን ወታደሮች በሳንጃ ያባርሯቸው ጀመር። ይህም የሀውልቶቹን መነሳት ተከትሎ የተፈጠረው የኢትዮጵያውያኑ ፀረ ፋሽስት ተአማኒ ስሜት ዜና የጣሊያን መንግስት ጋር ደርሶ ብስጭት ፈጠረ። ግራዚያኒም ከሳምንታት በኋላ በእርምጃ እንደተቆጣጠረው አሳወቀ። በወቅቱ የነበረ አንድ ስዊድናዊ ከአመት በኋላ እንደተናገረው፣ ኢትዮጵያውያኑ እርስ በእርሳቸው ስለጣሊያኖቹ “መንፈሱን እራሱ ይፈሩታል። አድዋን እኛ እንደምናስታውሰው ነው የሚያስታውሱት፤” እያሉ እንደሚንሾካሾኩ ምልከታውን ገልጿል። የኢትዮጵያውያኑም ተቃውሞ እና ትግል በየቦታው ቀጠለ።

እናም በዚህ ሁኔታ ከወራት በኋላ አብርሃና ሞገስ በዳግማዊ ምንሊክ ትምህርት ቤት ትምህርታቸውን ለመከታተል የመጡት። አብርሃ በጽኑ የጣሊያኖቹን ዘረኛ ተግባራት ይቃወም ስለነበር ትግሉን ተቀላቅሎ ግራዚያኒን ከግብረአበሮቹ ጋር ለመግደል ሙከራ ያደረገው። በግራዚያኒም አጸፋ ሰላሳ ሺህ ያህል ንጹሀን ተገደሉ፤ ክስተቱም በኢትዮጵያ ታሪክ እጅግ አስከፊ የነበረ ጭፍጨፋ ሆነ።

ለማጠቃለል፣ አዲስ አበባ ከአድዋ ድል ማግስት ከሁሉም የኢትዮጵያ ክፍሎችና ከውጭ ሀገራት በመምጣት ሀብትና ንብረት አፍርቶ እየኖረ የነበረው እንዲሁም በከተማዋ እየተበራከተ በመጣውና በተለያዩ የንግድ እና የማህበራዊ አገልግሎት ስራ መስኮች ላይ በተሰማራው የከተማዋ ነዋሪ ቅሬታ አማካኝነት አጼ ምኒሊክ ወደ አዲስ አለም ከተማ ሄዶ አዲስ መዲና የመቆርቆር እቅዳቸውን ሊቀለበስ ችሎ ነበር። በተመሳሳይ ሁኔታም፣ ከአርባ አመት በኋላ የጣሊያን መንግስት ኢትዮጵያን በወረረበት ጊዜ፣ በርካታ የሙሶሊኒ መንግስት አማካሪዎች አዲስ አበባን ትተው አዲስ ከተማ እንዲቆረቆር ቢጎተጉቱትም ሙሶሊኒ አሻፈረኝ በማለቱ አዲስ አበባም አሁን ላለችበት ትሩፋትና ማንነት የካቲት 12 እና በወቅቱ የነበረው የግራዚያኒ አስተዳደር የራሱን አሻራ ጥሎ ሊሄድ ችሏል። ለዚህም ነው የከተማ ቅርስ ስላለፈው ታሪካችን፣ ባህላችን እና ስለማህበረሰባችን ዝግመተ ለውጥ ፍንጮች የሚሰጠን መስኮት ነው የምንለው። ቸር እንሰንብት!

Interesing article?

Check out the full journal for other interesting contents and more.

Thank you for reading Ketema, the African building platform.

Subscribe below to receive an email when a new issue is released.

Your email address will not be shared with anyone else, and it’s easy to opt out if you change your mind.

© July, 2024 Ketema Journal

Thank you for reading Ketema, the urban building platform.

Subscribe below to receive an email when a new bimonthly issue is published.

Your email address will not be shared with anyone else, and it’s easy to opt out if you change your mind.

Seraphinite AcceleratorOptimized by Seraphinite Accelerator
Turns on site high speed to be attractive for people and search engines.